አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 23 2002 (ሬዲዮ ፋና) አዲሱ የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ ፍቃድ የማግኘት ሂደት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ መሆኑ ብልሹ አሰራርን በማስቀረት ረገድ ከፍተኛ ሚና ቢኖረውም ሊሻሻሉ የሚገባቸው ጉዳዮች አንዳሉ ተጠቆመ።
በየአመቱ ከ2 ሺ በላይ በሚሆኑ ሰዎች የሞት አደጋ ሲደርስ ግምቱ ከግማሽ ቢሊዮን ብር ያላነሰ ንብረት ይወድማል 8ሺ በሚሆኑ ወገኖች ላይም የአካል ጉዳት ይደርሳል።
አደጋውን ለመቀነስ የተለያዩ እርምጃዎች በተለያዩ ጊዜያት የተወሰዱ ቢሆንም የሚፈለገውን ውጤት ማምጣት አልተቻለም ከሁለት ዓመታት በፊት የወጣው አዋጅም ከነዚሁ እርምጃዎች አንዱ ነው።
አዋጁ መንጃ ፈቃድ የሚለውን ስያሜ ከመቀየር እስከ ስልጠናና የፈተና አሰጣጥ ስርዓት ለውጥ ያካተተና በመላ አገሪቱም ወጥነት ያለው የአሰራር ስርአት ለመዘርጋት የሚያስችል ነው።
በአጠቃላይ እስካሁን 100 የሚሆኑ ማሰልጠኛዎች እንዲሁም 26 ያህል ሰርተፊኬት የሚሰጡ ተቋማት በአዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተሞች አንዲሁም በሶሰት ክልሎች ይገኛሉ።
ይሁን እንጅ እስካሁን ለምን ያህሉ የአሽከርካሪነት ብቃት ማረጋገጫ ፈቃድ እንደተሰጣቸው የፌዴራል ትራንስፖርት ባለስልጣን የተጠናቀረ መረጃ የለውም።
አንድ ግለሰብ በቀጥታ የፈለገውን ተሽከርካሪ እንዲይዝ መፈቀዱን በሚመለከትም ዋናው ነገር አሽከርካሪው ለሚፈልገው የተሽከርካሪ ዓይነት ተገቢውን ስልጠና መውሰዱ መሆኑንና ሁሉም ተሽከርካሪዎች የየራሳቸው ባህሪ ስላላቸው አንድ ግለሰብ ለአንዱ የተሽከርካሪ ዓይነት ያወጣውን ፈቃድ ለሌላው መጠቀም እንደማይችል በፌዴራል ትራንስፖርት ባለስልጣን የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ የስራ ሂደት ዳይሬክተር አቶ ጸጋዬ መለሰ ገልጸዋል።
በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት አንዳንድ ግለሰቦች የጽሁፉም ሆነ የተግባር ፈተናው በኮምፒውተር የታገዘ መሆኑ ጥሩ ቢሆንም የጽሁፍ ፈተናው ይዘትና አቀራረብ ሊስተካከል እንደሚገባው ጠቁመው አንድ ሰው ብዙ ፍቃዶች እንዲኖሩት መደረጉ ለተጨማሪ ወጪ የሚዳርግ መሆኑን ገልጸዋል።
ወደ ተግባር ከተገባበት ካለፈው ዓመት ጀምሮ በአመዛኙ ትኩረት የተሰጠው ተቋማትን የማደራጀት ስራ መሆኑን አመልክተው አሰራሩ የታሰበውን ለውጥ ማምጣቱን የሚጠቁም ምንም አይነት ጥናት አለመደረጉን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
አሰራሩ የበርካታ አገሮችን ተሞክሮ መሰረት አድርጎ የተጀመረ ሲሆን በአሁኑ ወቅትም ከ150 በላይ አገሮች እየሰሩበት እንደሚገኙ የባልደረባችን በዛብህ ማሞ ዘገባ ያመለክታል።